ኦሪት ዘፍጥረት 33

1፤ ያዕቆብም ዓይኑን አነሣ፥ እነሆም ዔሳውን ሲመጣ አየው፥ ከእርሱም ጋር አራት መቶ ሰዎች ነበሩ፤ ልጆቹንም ከፍሎ ወደ ልያና ወደ ራሔል ወደ ሁለቱም ባሪያዎች አደረጋቸው፤

2፤ ባሪያዎችንና ልጆቻቸውንም በፊት አደረገ፥ ልያንና ልጆችዋንም በኋለኛው ስፍራ፥ ራሔልንና ዮሴፍንም ከሁሉ በኋላ አደረገ።

3፤ እርሱም በፊታቸው አለፈ፤ ወደ ወንድሙም እስኪደርስ ድረስ ወደ ምድር ሰባት ጊዜ ሰገደ።

4፤ ዔሳውም ሊገናኘው ሮጠ፥ አንገቱንም አቅፎ ሳመው፤ ተላቀሱም።

5፤ ዓይኑንም አነሣና ሴቶችንና ልጆችን አየ፥ እንዲህም አለ። እነዚህ ምኖችህ ናቸው? እርሱም። እግዚአብሔር ለእኔ ለባሪያህ የሰጠኝ ልጆች ናቸው አለ።

6፤ ሴቶች ባሪያዎችም ከልጆቻቸው ጋር ቀርበው ሰገዱ፤

7፤ ደግሞም ልያና ልጆችዋ ቀርበው ሰገዱ፤ ከዚያም በኋላ ዮሴፍና ራሔል ቀርበው ሰገዱ።

8፤ እርሱም። ያገኘሁት ይህ ሠራዊት ሁሉ ምንህ ነው? አለ። እርሱም። በጌታዬ ፊት ሞገስን አገኝ ዘንድ ነው አለ።

9፤ ዔሳውም። ለእኔ ብዙ አለኝ፤ ወንድሜ ሆይ፥ የአንተ ለአንተ ይሁን አለ።

10፤ ያዕቆብም አለ። እንደዚህ አይደለም፤ ነገር ግን በፊትህ ሞገስን አግኝቼ እንደ ሆንሁ እጅ መንሻዬን ተቀበለኝ፤ የእግዚአብሔርን ፊት እንደሚያይ ፊትህን አይቼአለሁና፥ በቸርነትም ተቀብለኸኛልና።

11፤ ይህችንም ያመጣሁልህን በረከቴን ተቀበል፤ እግዚአብሔር በቸርነት ሰጥቶኛልና፥ ለእኔም ብዙ አለኝና። እስኪቀበለውም ድረስ ዘበዘበው።

12፤ እርሱም። ተነሣና እንሂድ፥ እኔም በፊትህ እሄዳለሁ አለ።

13፤ እርሱም አለው። ጌታዬ ሆይ፥ ልጆቹ ደካሞች እንደ ሆኑ ታውቃለህ፤ በጎችና ላሞችም ግልገሎቻቸውን ያጠባሉ፤ ሰዎችም አንድ ቀን በችኮላ የነዱአቸው እንደ ሆነ ከብቶቹ ሁሉ ይሞታሉ።

14፤ ጌታዬ ከባሪያው ፊት ቀድሞ ይለፍ፤ እኔም ወደ ሴይር ከጌታዬ ዘንድ እስክደርስ ድረስ ከፊቴ ባሉት በእንስሳቱ እርምጃና በሕፃናቱ እርምጃ መጠን በዝግታ እከተላለሁ።

15፤ ዔሳውም። ከእኔ ጋር ካሉት ሰዎች ከፍዬ ልተውልህን? አለ። እርሱም። ይህ ለምንድር ነው? በጌታዬ ዘንድ ሞገስን ማግኘት ይበቃኛል አለ።

16፤ ዔሳውም በዚያን ቀን ወደ ሴይር መንገዱን ተመለሰ።

17፤ ያዕቆብ ግን ወደ ሱኮት ሄደ፤ በዚያም ለእርሱ ቤትን ሠራ፥ ለከብቶችም ዳሶችን አደረገ፤ ስለዚህም የዚያን ቦታ ስም ሱኮት ብሎ ጠራው።

18፤ ያዕቆብም ከሁለት ወንዞች መካከል በተመለሰ ጊዜ በከነዓን ምድር ወዳለችው ወደ ሴኬም ከተማ በደኅንነት መጣ፤ በከተማይቱም ፊት ሰፈረ።

19፤ ድንኳኑን ተክሎበት የነበረውንም የእርሻውን ክፍል ከሴኬም አባት ከኤሞር ልጆች በመቶ በጎች ገዛው።

20፤ በዚያም መሠውያውን አቆመ፥ ያንም ኤል ኤሎሄ እስራኤል ብሎ ጠራው።