0:00

መዝሙረ ዳዊት 47

1 ለመዘምራን አለቃ፤ የቆሬ ልጆች መዝሙር። 1 አሕዛብ ሁላችሁ፥ እጆቻችሁን አጨብጭቡ፥ በደስታ ቃልም ለእግዚአብሔር እልል በሉ።

2 እግዚአብሔር ልዑል ግሩምም ነውና፥ በምድር ሁሉ ላይም ታላቅ ንጉሥ ነውና።

3 አሕዛብን ከእኛ በታች፥ ወገኖችንም ከእግራችን በታች አስገዛልን።

4 ለርስቱ እኛን መረጠን፥ የወደደውን የያዕቆብን ውበት።

5 አምላክ በእልልታ፥ እግዚአብሔር በመለከት ድምፅ ዐረገ።

6 ዘምሩ፥ ለአምላካችን ዘምሩ፤ ዘምሩ፥ ለንጉሣችን ዘምሩ።

7 እግዚአብሔር ለምድር ሁሉ ንጉሥ ነውና፤ በማስተዋል ዘምሩ።

8 እግዚአብሔር በአሕዛብ ላይ ነገሠ፤ እግዚአብሔር በቅድስናው ዙፋን ይቀመጣል።

9 የምድር ኃይለኞች ለእግዚአብሔር ናቸውና የአሕዛብ አለቆች ወደ አብርሃም አምላክ ተሰበሰቡ፤ እርሱንም ከፍ ከፍ አደረጉት።